Wednesday, October 31, 2012

የፍርሐት ዘመን

ማሕሌት ፋንታሁን

በሕይወታችን የምናደርጋቸውን እንቅስቃሴዎች ከመከወን እንድንቆጠብ ለራሳችን ስንነግር ወይም ውስጣችን ሲሰማው የፍርሐት ስሜት ተሰማን ልንል እንችላለን፡፡ የፍርሐትን ምንጭ በሁለት ከፍለን ማየት እንችላለን፡፡ የመጀመሪያው ፍርሐታችንን የምናምንበት፣ ምክንያቱም ከራሳችን የመነጨ ድክመት በሚሆንበት ጊዜ ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ድርጊቱን በመፈፀማችን ሊደርስብን ይችላል ብለን የምናሰላው አግባብ ያልሆነ ጉዳት/በደል በማሰብ ድርጊቱን ከመፈፀም ስንቆጠብ ነው፡፡

ከላይ እንዳልኩት የለት ተለት እንቅስቃሴዎቻችን ውስጥ ምንጫቸው ከሁለት አንዱ ወይም ከሁለቱም የሆነ ፍርሐት ሊያሳድሩብን የሚችሉ ጉዳዮች ብዙ ናቸው፡፡ ይህ ጽሑፍ የሚያጠነጥነው በአሁን ሰዓት በሀገራችን የሚታየውን የፖለቲካ ጉዳዮች ላይ ሐሳብን የመሰንዘር፣ የመወያየት፣ የመሳተፍ እና የመተቸት ፍርሐትን ሲሆን፤ በሁለተኛ ደረጃ ደግሞ በተጠቀሰው የፍርሐት ምንጭ የሚከሰተውን ነው፡፡

ተማሪዎች

ተማሪዎች ስል ዕድሜያቸው ለአቅመ ማገናዘብ ከደረሱት ጀምሮ ማለቴ ነው፡፡ እነዚህ ተማሪዎች ወደ ከፍተኛ ትምህርት ለመግባት ዕድሉ ያላቸው ወይም ለቴክኒክና ሙያ ስልጠና የሚገቡ ወይም በግል ኮሌጅ ገብተው የሚቀጥሉና ውጤታቸው ትምህርታቸውን የማያስቀጥላቸው ሲሆኑ ሁሉንም የሚያመሳስላቸው አንድ ነገር አለ፡፡ ትምህርታቸውን የቀጠሉትም ያልቀጠሉትም በደረጃቸው ሥራ የመያዝ እና ራሳቸውን ለማኖር የመጣር ግዴታ አለባቸው፡፡ ሥራ ለማግኘት ደግሞ ያልተጻፈው ሕጋችን በኢሕአዴግ መጠመቅን ይጠይቃል፡፡ ሥራ አጥ ሆኖ ኢሕአዴግን መቃወም ወይም ስህተቶቹን እየነቀሱ መተቸት የማይታሰብ ነው፡፡ ይህን ጠንቅቀው ስለሚያቁ  ተማሪዎች ቀደም ብለው አባል ወይም በደጋፊነት መዝገብ መስፈርትን እና የሚፈለገውን ሟሟላት ሌላው ተግባራቸው ይሆናል፡፡ ምክንያቱም ዋናው ነገር እንጀራ ነው፡፡ ምናልባትም ከተደላደሉና የትም ተቀጥረው የመሥራት ዕድላቸው የሰፋ ሲሆን ወደራሳቸው ሊመለሱ የሚችሉ ቢሆንም በጣም ኢሕአዴግ በሆኑ ቁጥር ጥቅማ ጥቅሞቹም በዛው ልክ ስለሚጨምሩ እዛው ሰምጠው የሚቀሩ ይበዛሉ፡፡ ለዚህም ነው በብዙ መጽሐፍት ያነበብነውን የሀገራቸውን ፖለቲካ የሚተነትኑ እና የራሳቸው የሆነ አቋም ያላቸው ተማሪዎች ማየት ሕልም የሆነብን፡፡

Sunday, October 28, 2012

“ጠንቅቆ” የመጻፍና አለመጻፍ ጉዳይ


በእንግሊዝኛው spelling ወይንም orthography የሚባለውን ፕሮፌሰር አምሳሉ አክሊሉ “ጠንቅቆ መጻፍ” ሲሉ ሠይመውታል፡፡ ጠንቅቆ መጻፍ በአማርኛ ቋንቋ ትክክለኛውን ሆሄ በትክክለኛው ቃል ላይ መጠቀምን ይመለከታል፡፡


ስንጽፍ ‘መጽሀፍ፣መጽሃፍ፣ መጽሐፍ፣ መጽሓፍ፣ መጽኀፍ፣ መጽኃፍ፣ መጽኻፍ፣ መፅሀፍ፣ መፅሃፍ፣ መፅሐፍ፣ መፅሓፍ፣ መፅኀፍ፣ መፅኃፍ፣ መፅኻፍ’ ከሚለው ውስጥ የትኛው ነው ትክክል ከሚለው ጥያቄ አንስቶ፥ ትክክለኛው ቃል ከታወቀ በኋላ ያንን ቃል በተጠቀሙ ቁጥር ለማስታወስ መቸገሩ፣ ያንኑ የሆሄ አጠቃቀም በርቢዎቹ ላይ (መጽሐፍ፣ ጸሐፊ፣ ጽሕፈት…) ላይ ለመተግበር እስከማስታወስ ድረስ በፈታኝ ሁኔታ ውስጥ ማለፍ የግድ ነው፡፡

ሰሞኑን ከኢቴቪ እስከ ፍትሕ/አዲስ ታይምስ… ከፍትሕ/አዲስ ታይምስ እስከ ፌስቡክ ቃላትን በትክክለኛ ሆሄያቸው የመጠቀም እና ያለመጠቀም፣ ተደጋጋሚ ደምፅ ያላቸውን ሆሄያት የማስወገድ እና ያለማስወገድ ጉዳይ በጣም እያወያየ ነው፡፡

ችግሩን መፍትሔ የሌለው ወይም ክርክሩ ማቧሪያ የሌለው የሚያስመስለው ደግሞ በተለይ በአማርኛ ቋንቋ ውስጥ የሆሄያቱ መቀያየር የድምፅ እና የትርጉም ልዩነት የማያመጣ መሆኑ ነው፡፡ (ይህ ዓይነቱ ልዩነት ግን በግዕዙ ውስጥ የተለመደ ነው) ሌላኛው የአይቀነስ ባዮች መከራከሪያ ነጥብ ደግሞ “መቀነስ ምን ይጠቅማል?” የሚል እና “ከዚህ በፊት የተዘጋጁ እና የተከማቹ መዝገቦች እና ድርሳናት ማንበብ ይቸግራል” የሚል ነው፡፡

ለነዚህ ጥያቄዎች አጥጋቢ መልስ መስጠት በጣም አስቸጋሪ ይሆናል፡፡ በርግጥ የሆሄያቱ መብዛት ለቋንቋው ቴክኖሎጂካል አገባብ (በተለይ ከኮምፒዩተር የቁልፍ ሰሌዳ አቀማመጥ አንጻር አስቸጋሪ እየሆነ ስለሆነ) ቢቀነስ ይጠቅማል  ማለትም ይቻላል፡፡ የሆነ ሆኖ የዚህ ዓይነቱ ክርክር ሰሞኑን የተፈጠረ አለመሆኑን የሚያረጋግጥ መጽሐፍ እጃችን የገባው፥ ለዞን ዘጠኝ የቋንቋ ዘዬ እያዘጋጀን ሳለን ነበር፡፡

Thursday, October 25, 2012

‘ሰንደቁ’ ላይ ያለው ‘አላማ’


ወቅቱ የኢትዮጵያ ህዝቦች አብዮታዊ ዲሞክራሲያዊ ግንባር (ኢህአዴግ) ስልጣን በያዘበት ማግስት ነው፡፡ በጊዜው የነበረው የሀገሪቱ ሰንደቅ ዓላማ አረንጓዴ፣ ቢጫ እና ቀይ ቀለማትን ብቻ ያዘ ነበር (በርግጥ በሕግ የተደነገገ ባይሆንም በአንዳንድ የደርግ ተቋማት ውስጥ ሰማያዊ መደብ ያለው ሰንደቅ ዓላማም ይስተዋል ነበር)፡፡ የወቅቱ ባለስልጣናትም  አረንጓዴ፣ ቢጫ እና ቀዩ ሰንደቅ ዓላማ ላይ የብሄሮችን መፈቃቀድ የሚገልፅ አርማ መኖር አለበት፤ አርማውስ ምን አይነት ይሁን? የሚል ሃሳብ ይቀርባሉ፡፡ የታሪክ ፕሮፌሰር የሆኑት ላጲሶ ጌ. ዴሌቦም ሀሳባቸውን እንደሚከተለው ሰነዘሩ ‹‹የኢትዮጵያ ሕዝብ በጣም ተጨቁኖ የኖረ ሕዝብ ነው፡፡ ስለዚህም በሰንደቅ ዓላማው ላይ የሚቀመጠው አርማ ይሄን ጭቆናውን የሚገልፅ መሆን ይኖርበታል፡፡ ለዚህም ደግሞ ‘ከአህያ ምስል’ የተሻለ አርማ የለም፡፡ ሕዝቡ እንደ አህያ ለዘመናት አምባገነንነት ተጭኖበት በጭቆና ውስጥ ነበርና፡፡››  

ይህ ከሆነ 17 ዓመታት በኋላ ተሻሽሎ የወጣው የሰንደቅ ዓላማ አዋጅ ቁጥር 654/ 2001 በአንቀፅ 4 ላይ እንዳሰፈረው ‹‹ብሄራዊ የሰንደቅ ዓላማ ቀን በየዓመቱ መስከረም ሁለኛ ሳምንት ሰኞ በድምቀት ይከበራል፡፡›› ከአዋጁ መውጥት አስቀድሞ በሰኔ 2000 ዓ.ም በግለሰቦች አነሳሽነት መከበር የጀመረው የሰንደቅ ዓላማ ቀን ዘንድሮ ለ5ኛ ጊዜ  ሰንደቃላማችንን ከፍ አድርገን  በመለስ ቀያሽነት የተጀመረውን ህዳሴ እናረጋግጣለን!” እንደሚከበር ተገልል፡፡ ነገር ግን የዘንድሮው ክብረ በዓል በአዋጁ ከተደነገገው ቀን አልፎ ጥቅምት 19/2005 ዓ.ም ነው  የሚከበረው፤ ይሄን አስመልክተን በኢትዮጵያ  ሰንደቅ አላማ ዙሪያ ያሉ ሀተታዎችን ለመመልከት ተነሳን፡፡

ሰንደቅ ዓላማ

ከሰንደቅ አላማ ቀለም እና ምልክት ጀርባ ታሪክ፣ ባህል፣ ማንነት እንዲሁም አንዳንዴ አስተሳብን የሚያመለክት መንፈስ አለ፡፡  የካውካሲያን ህዝቦችን (ለምሳሌ የአሜሪካ፣ የእንግሊዝ፣ የፈረንሳይ፣የሩስያ፣ የአውስትራሊያ ወ.ዘ.ተ)  ሰንደቅ አላማዎችን ብንመለከት በአብዛኛው ነጭ፣ ቀይ እና ሰማያዊ ቀለማትን ለሰንደቅ አላማነት ይጠቀማሉ፡፡ የቀለማቱም ምርጫ በተወሰነም መልኩ የህዝቦቹን አንድ አይነት አመለካከት ይገልፃሉ፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ የአፍሪካዊያንን ሰንደቅ ዓላማ ስንመለከት አረንጓዴ፣ ቢጫ እና ቀይ ቀለማት ከፍ ብለው እና በተለያየ አደራደር ተቀምጠው እናያለን፡፡ ይሄም ተመሳሳይ ምክንያት እንዲሸተን ያደርገናል፡፡

ታሪክ ወ አፈታሪክ  

የሀገራችን የኢትዮጵያ ሰንደቅ አላማ በሀገሪቱ ውስጥ አነታራኪ ከሚባሉ ጉዳዮች አንዱ ነው፡፡ ንትርኩም የሚጀምረው ከታሪካዊ አመጣጡ ጀምሮ ነው፡፡ በዚህም ጉዳይ ታሪክን ከአፈታሪክ (History from Myth) ለመለየት አስቸጋሪ ከመሆኑ አንፃር በዋነኛነት ጎልተው የሚሰሙትን ታሪኮች እና አፈታሪኮችን አዳቅለን ለማየት እንሞክር፡፡

በአሁኑ ወቅት ያለውን የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ ለምን አረንጓዴ፣ ቢጫ እና ቀይ ቀለማት ሊሆን ቻለ? ለሚለው መልስ የተለያ ወገኖች የተለያዩ ምክንያቶችን ያቀርባሉ፡፡ ክርስቲያናዊ ትርጉሙም ገዝፎ ይታያል፡፡ እንደ አንዳንድ ፀሃፍት ‹‹የቀድሞ አባቶቻችን እና እናቶቻችን ወደ ጦር ሜዳ ሲሄዱ የተለያዩ የዛፍ ዝንጣፊዎችን ይዘው ይዘዋወሩ ነበር፡፡ የሚይዙት ዝንጣፊም አረንጓዴ በመሆኑ በተለያዩ ነገሮች አረንጓዴ ነገርን በማዘጋጀት እንደ ቀዳሚው የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ ሆነ፡፡›› በማለት አጀማመሩን ይገልፃሉ፡፡

አፈታሪኩ ሲያስከትልም ‹‹ኢትዮጵያ ከሕገ ልቦና ወደ ሕገ ኦሪት በንግስተ ሳባ አማካኝነት ስትሸጋገር በእግዚአብሄር ተስፋ ማድረግን ለማመላከት ኢትጵያዊያኑ ቀድመው ይጠቀሙበት የነበረው አረንጓዴ መለያ ላይ ቢጫ ቀለምን በመጨመር አንድ እርምጃ ወደፊት ተሻገ›› በማለት ክልኤቱ ይላል፡፡ ክርስቲያናዊ አፈታሪኩ ሲቀጥልም ‹‹በንጉስ ባዚን ጊዜ ወደ እየሩሳሌም አቅንቶ ወንጌልን አውቆ የተመለሰው ኢትዮጵያዊው ጃንደረባ ክርስትናን ወደ ኢትዮጵያ ይዞ ከመግባቱ ጋር ተያይዞ፤ ኢትዮጵያዊያን እየሱስ ክርስቶስ በደሙ ቤዛ እንደሆናቸው በማመናቸው ቀድመው ይጠቀሙበት የነበረውን አረንጓዴ እና ቢጫ መለያ ላይ ቀይ ቀለም በመጨመር አሁን ያለውን ቀለም እንዲይዝ አድርገውታል›› ይላል፡፡

በሌላ በኩል ደግሞ የኢትዮጵያ ሰንደቅ አላማ አረንጓዴ፣ ቢጫ እና ቀይ የሆነው እግዚአብሄር አለምን ዳግም በጥፋት ውሃ ላለመምታት ለኖህ የገባውን ቃልኪዳን የፈፀመው በቀስተዳመና ነው፤ በቀስተ ዳመናውም ውስጥ ገዝፈው የሚወጡት ቀለሞች አረንጓዴ፣ ቢጫ እና ቀይ በመሆናቸው የነሱን አምሳያነት ነው የሚል አፈታሪክ ይደመጣል፡፡ ከዚሁ ከኖህ ጋር ተያይዞ ‹‹የጥፋት ውሃው በጎደለ ጊዜ እንደ ብስራት መግለጫ የታየው የወይራ ቅጠል መጀመሪያ አረንጓዴ፣ ሲቆረጥ ወደ ቢጫ በመቀየር መጨረሻ ላይ ቀይ ቀለምን በመያዝ ይደርቃል እናም ሰንደቅ ዓላማችን የወይራው ተምሳሌት በመሆን መልካም ዜናን ገላጭ ነው›› የሚል አፈታሪክም ይደመጣል፡፡

የቅርብ ጊዜ ታሪኮች ደግሞ የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ የአሁኑን ቀለም የያዘው ባለፍት 150 ዓመታት በተደረገው ክለሳ ነው፡፡ ከዛ በፊት የነበረው ሰንደቅ ዓላማ ሌሎች የተለያዩ ቀለማትን የያዙ ነበሩ ይሉናል፡፡ ነገር ግን አንዳንዶች በአፄ ቴዎድሮስ ሁለተኛ ጊዜ ነው የአሁኖቹ ቀለማት ጥቅም ላይ የዋሉት ሲሉ፤ ሌሎች ደግሞ የለም የለም በአፄ ዩሃንስ አራተኛ ዘመነ መንግስት ነው ይላሉ፣ በሌላ በኩል ደግሞ አይ በዳግማዊ ምኒልክ ንግስና ዘመን ነው፤ ይህ የሆነው በማለት ታሪኩን ያወሳስቡታል፡፡ እንግዲህ የቀለማቱ ታሪክ እና ትርጉም ስምምነት ላይ ሳይደረስበት ሲሰረዝ እና ሲደለዝ አሁን የምንጠቀምበትን አረንጓዴ፣ ቢጫ እና ቀይ ቀለማት በሰማያዊ አርማ እና በቢጫ ኮከብ የታጀበ ሰንደቅ ዓላማ ላይ ደርሰናል፡፡ ውዝግቡ ግን አሁንም እንደቀጠለ ነው፡፡ እስኪ በአሁኑ ወቅት በሰንደቅ ዓላማ ጉዳይ ላይ የሚነሱትን አንዳንድ የውዝግብ ነጥቦች እያነሳን እንመልከት፡፡

ሰንደቅ ዓላማ ወይስ ሰንደቅ ዓላማዎች?

ከጣሊያን ወረራ በማስከተል በተፈጠረው አጋጣሚ ኢትዮጵያ የቀድሞ የግዛት አካሏን እና ለ50 ዓመታት በጣሊያን ቅኝ ግዛት ምክንያት ተነጥሎ የኖረውን የግዛት ክፍሏ ይመለስላት ዘንድ ለተባበሩት መንግስታት ድርጅት አመለከተች፡፡ የተባበሩት መንግስታት ድርጅትም ከረጅም እና አታካች ውይይት እና ግምገማ በኋላ በአሜሪካን መንግስት አነሳሽነት ኤርትራ ከኢትዮጵያ ጋር በፌደሬሽን እንድትዋሃድ ወሰነ፡፡ ኢትዮጵያም በውሳኔው ለጊዜው ግር ብትሰኝም እንደ አሜሪካን እና ህንድ አይነት ታላላቅ ሀገሮችም በዚሁ የፌደሬሽን ስርዓት እንደሚመሩ መገለፁ ብዥታውን እንዲያለዝበው ሆነ፡፡

ነገር ግን በብዙ ኢትዩጵያውያን እና በኤርትራ የሚገኝው የአንድነት ማህበር (The Unionist Party) ፤ ኤርትራ ከሌላው የኢትዮጵያ ክፍል ተለይታ የራሷን ሰንደቅ ዓላማ ማውለብለቧ አልተዋጠላቸውም ነበር፡፡ ይሄም ነገር ይቀለበስ ዘንድ አብዝተው በመጎትጎታቸው ለ10 ዓመታት የቆየው ፌደሬሽንም በንጉሱ ፊርማ ፈረሶ የኤርትራ ሰንደቅ ዓላማም ጉዳይ አከተመ፡፡

የኢህአዴግን ስልጣን መያዝ ተከትሎ የኤርትራ መገንጠል ብዙ ኢትዮጵያዊያንን ያስደነገጠ ጉዳይ ነበር፡፡ በሽግግር መንግስቱ ወቅት ተረቆ የፀደቀው የኢፌደሪ ሕገ መንግስት ፌደራሊዝምን እንደ መንግስታዊ መዋቅር መቀበሉ ደግሞ አንዳንድ ወገኖች በተለይም አጥባቂ ኢትዮጵያዊንን (Ultranationalists) ‹‹ይህች ሀገር ተገነጣጥላ ልታልቅ ነው›› የሚል ሌላ ስጋት ውስጥ ከተታቸው፡፡

ሕገ መንግስቱ የፌደራል ስርዓቱ በክልልሎች እንደሚዋቀርና እያንዳንዱ ክልሎችም የራሳቸው የሆነ ሰንደቅ ዓላማ እና አርማ እንደሚኖራቸው መደንገጉ፤ ለነዚህ ወገኖች የኢህአዴግን ፀረ-ኢትዮጵያዊነት መረጋገጫ ነበር፡፡ ኢህአዴግ በበኩሉ ‹‹ፌደራሊዝሙ እንደዚህ ካልተዋቀረ አብረን መኖራችን ያሰጋናል፤ ክልሎች የራሳቸው ሰንደቅ ዓላማ እና ዓርማ እንዲኖራቸው መፍቀዱ ደግሞ አሜሪካን በሚያክል ትልቅ ሀገር ሳይቀር ተቀባይነት ያለው የራስን በራስ የማስተዳደር አንዱ መገለጫ ነው፡፡ ኢትዮጵያም በተወሰኑ ቀለማት ብቻ አትገለፅም፡፡›› የሚሉ ምላሾችን በመስጠት ለክልሎች የራሳቸውን ሰንደቅ ዓላማዎች እንዲመርጡ አስቻላቸው፡፡

ከዛን ጊዜ ወዲህ የሱማሌ ክልል ባለፉት ሁለት አስርት ዓመታት ጊዜ ውስጥ ወደ 11 ርዕሰ መስተዳደሮችን የቀያየረ ሲሆን፤ በሰንደቅ ዓላማ መቀየሩስ ለምን ይቅርብኝ? በሚመስል ምክንያት ሁለት የተለያዩ ሰንደቅ ዓላማዎችን ቀይሯል፤ ይሄም ድርጊት ብዥታን መፍጠሩ አልቀረም፡፡ በሌላ በኩል የትግራይ ክልል ሰንደቅ ዓላማ ህወሃት በትግል ወቅት ይጠቀምበት የነበረው ሰንደቅ ዓላማ  ለትግራይ ክልልም ማበርከቱ ትክክል አይደለም የሚል ሀሳብ መነሳቱ አልቀረም፡፡

እንግዲህ አንድ ሀገራዊ ሰንደቅ ዓላማ? ወይስ ሁሉም ክልሎች ከሀገራዊ ሰንደቅ ዓላማው ጎን ለጎን የሚያውለበልቡት የራሳቸው ሰንደቅ ዓላማዎች? የሚለው ሃሳብ አነታራኪነቱን ይዞ ቀጥሏል፡፡

‹‹ባንዲራ ጨርቅ ነው ... አንዳንድ ሀገሮች ከወረቀትም ይሰሩታል››

ባለፉት ዓመታት ሰንደቅ ዓላማ በተነሳ ቁጥር የቀድሞው የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ መነሳታቸው አልቀረም፡፡ በአንድ ወቅት ‹‹ባንዲራ ጨርቅ ነው›› ማለታቸው እንደ አንድ ሀገሩን የማይወድ መሪ እንዲቆጠሩ ያደረጋቸው ሲሆን፤ ከብዙ ኣመታት በኋላ ‹‹ባንዲራ ጨርቅ ነው›› ሲሉ ምን ማለታቸው እንደሆነ ሲጠየቁ፤ ‹‹አዎ ባንዲራ ትርጉም ከሌለው እንደወረደ ጨርቅ ነው፤ እንዲያውም አንዳንድ ሀገሮች ከወረቀት ይሰሩታል፡፡ ባንዲራ ትርጉም ይኖረው ዘንድ ዜጎች ሊወዱት እና ትርጉም ሊሰጡት ይገባል፡፡›› በማለት ምክንያታቸውን ለማቅረብ ሞክረዋል፡፡

 ነገር ግን ማሳመኛቸው ያልተዋጠላቸው ሰዎች ‹ምንም ቢሆን እንደ ሀገር መሪ እንደዚህ ማለት አልነበረባቸውም›› በማለት ሀሳባቸውን ያጣጥሉባቸዋል፤ አቶ መለስንም በፀረ-ኢትዮጵያዊነት ይፈርጇቸው ነበር፡፡ መለስ ግን ከቅርብ ዓመታት ወዲህ እንደ ሰንደቅ ዓላማ ቀን ባሉ በዓላት ላይ በመገኝት  ስማቸውን ለማደስ መጣራቸው አልቀረም ነበር፡፡

The Magic Emblem

ሌላው በአሁኑ ወቅት በሰንደቅ ዓላማ ጉዳይ ላይ ጎልቶ የሚነሳው ክርክር፤ በአሁኑ የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ ላይ ያለው አርማ ምንነት እና ትርጉም ነው፡፡ ለዛም ይመስላል ጉራማይሌ የሆነ የሰንደቅ ዓላማ አይነት በየቦታው የምንመለከተው፡፡ የኢፌዴሪ ሕገ መንግሰት በአንቀፅ 3 ንዑስ አንቀፅ 2 ላይ እንዲሁም ተሻሽሎ የወጣው የሰንደቅ ዓላማ አዋጅ 654/2001 በአንቀፅ 8 ላይ እንዳስቀመጡት በሰንደቅ ዓላማው ላይ ያለው ዓርማ ሰላምን፣ እኩልነትን አንድነትን እና ተስፋን ገላጭ እንደሆነ ያስረዳሉ፡፡
ይህ ትርጉም  ያልተዋጠላቸው ወገኖች ምልክቱን በብዙ መልኩ በመተርጎም በህገ መንግስቱም ሆነ በአዋጁ የተጠቀሱት የአርማው ምክንያት ውሸት ነው ይልቅስ ‹‹የአንድ ብሄርን የምግብ አይነት አመላካች ነው›› ፣ አይ ‹‹ምልክቱ የኢህአዴግ አመራሮች ከሶሻሊዝም ምንጭ እየጠጡ (From Socialism Background) የጎለመሱ በመሆናቸው የሶሻሊዝሟን ኮከብ በአቋራጭ ሰንደቅ አላማዋ ላይ ማስቀመጣቸው ነው፡፡›› ይላሉ፡፡ ይባስ ብሎም አንዳንዶች ‹‹የጥንቆላ ምልክት ነው፤ እንጅማ የኮከብ ምስል ከኢትዮጵያ ጋር ምን አገናኝው?››› ይላሉ፡፡

የሆነ ሆኖ የሰንደቅ ዓላማ አዋጁ በሕገመንግስቱ ከተቀመጠው ዓርማ ውጭ የተሰራ ሰንደቅ ዓላማን መጠቀም እስከ አንድ አመት በሚደርስ ፅኑ እስራት የሚያስቀጣ መሆኑን የሚደነግግ ሲሆን፤ የኮከቡን አርማ ከያዘው ሰንደቅ አላማ ውጭ ያሉ ታሪካዊ ሰንደቅ ዓላማዎች በቤተ መዘክር እንደሚቀመጡ እና በአረጁ ጊዜም እንደሚቃጠሉ ይገልፃል፡፡

ዳግማዊ ቦሊቪያን መቅደም

በንጉሱ ዘመን የነበረው የኢትዮጵያን ሰንደቅ አላማ በአንዳንድ የትርጉም ምክንያቶች ከአረንጓዴ፣ ቢጫ እና ቀይ ወደ ቀይ ቢጫ እና አረንጓዴነት ለመቀየር ኢትዮጵያ ለተባበሩት መንግስታት ድርጅት አመልክታ ይህ አደራደር በደቡባ አሜሪካዊዋ ሀገር ቦሊቪያ የተያዘ መሆኑን ተገልጾ ጥያቄዋ ውድቅ ተደርጎባታል፡፡

እንደ መላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) ያሉ የፖለቲካ ፓርቲዎች ሰማያዊ አርማ የሌለበትን ንፁህ አረንጓዴ፣ ቢጫ እና ቀይ ሰንደቅ ዓላማ እንደ ትክክለኛው የኢትዮጵያ ሰንደቅ አላማ በመቁጠር፤ በፓርቲያቸው ፕሮግራም ውስጥ ያካተቱ ሲሆን ለተባበሩት መንግስታት ድርጅትም የቦሊቪያው ታሪክ እንዳይደገም ይሄን ቀለም የያዘ ሰንደቅ ዓላማ ለሌላ ሀገር እንዳይፈቅድ እስከ መጠየቅ ደርሰዋል፡፡

የሀገራችን ፖለቲካ ፓርቲዎች በሰንደቅ ዓላማ ጉዳይ ላይ እንኳን ስምምነት ላይ አልደረሱም፡፡ ለየትኛው ሰንደቅ አላማም ክብር (Allegiance) እንደሚሰጡም አልተስማሙም፡፡ ይህ ልዩነት ህብረተሰባችን ውስጥም አለ፡፡ ብቸኛው መፍትሄ ወደ ውይይት ቀርቦ ሀሳብን መሸጥ እና መግዛት ነው፡፡ ያለዚያ የተለያየ ሰንደቅ ዓላማ ይዘን የኢትዮጵያን ጥቅም በጋራ ማስጠበቅ እንዴት ይቻለናል?

Wednesday, October 24, 2012

የእነርሱ እና የእኛ ሕዳሴ




የሐዲስ ዓለማየሁን “ጉዱ ካሣ”፣ የበዓሉ ግርማን “አበራ”፣ የዳኛቸው ወርቁን “አደፍርስ” ማን ይዘነጋቸዋል? እንኳን ‘ፍቅር እስከመቃብር’ን፣ ‘ከአድማስ ባሻገር’ን እና ‘አደፍርስ’ን ያነበቡ ቀርቶ ያላነበቡም ያውቋቸዋል፡፡ እነዚህ ገጸ ባሕርያት የሚታወሱት ከዘመናቸው ባፈነገጠ ማኅበራዊ ሃያሲነታቸው ነው፡፡

እነዚህን ገጸ ባሕርያት ወደኋላ ዞር ብለን የፈጠሯቸውን ደራሲያን ስናስብ ደራሲያኑ በየገጸ ባሕሪዎቻቸው አንደበት ማኅበረሰቡን በነገር አለንጋ ይገርፉታል፣ በምክንያት ይሞግቱታል፡፡ ያኔ እነዚህ እና ሌሎቹም ጸሐፍት ይህንን አሉ፤ ዛሬ እና የዛሬዎቹስ?

እዚህች’ጋ ሌላው የዞን ዘጠኝ ጦማሪ ባለፈው ሣምንት የጠየቃትን ጥያቄ መልኳን ቀይሬ ላንሳትና፣ እንደው ለመሆኑ (ከዚሁ ከልቦለድ ዘርፍ ሳንወጣ) በአለፉት አምስት፣ አሥር ወይም ሀያ ዓመታት ውስጥ እጅግ ተወደደ አነጋገረ፣ ልቤ ውስጥ ቀረ የምንለው መጽሐፍ አለ? ከላይ የጠቀስናቸውን ገጸ ባሕርያት ያክል ያመራመረን፣ ያነጋገረን፣ የሚታወሰን ገጸ ባሕሪ አለ? - ለኔ የለም፡፡

ጥያቄውን በልቦለድ ብቻ አነሳሁት እንጂ፣ ከአንድ ወዳጄ’ጋ ከዚህ ቀደም በመሰል ሐሳቦች ዙሪያ ስናወራ፤ እስኪ የ60ዎቹን ዘመን ወጣቶች እና የአሁኖቹን እናወዳድር ብለን በሁሉም ዘርፍ ሞክረን ነበር፡፡ ያኔ የነበሩ ወጣት ደራሲያኖችን እና ገጣሚዎቻችንን ጠቃቀስን እና አሁን ላይ መጣን… ከበውቀቱ ስዩም እና ምናልባትም እንዳለ ጌታ ከበደ በላይ መሻገር አልቻልንም፡፡ እነአፈወርቅ ተክሌ፣ እነእስክንድር ቦጎሲያን እና ወዘተን… ጠቃቀስን እና የነርሱ እኩያ ይሆናሉ ብለን ተስፋ የምንጥልባቸውን ሰዓሊዎች ማፈላለግ ጀመርን፣ ይሄ ነው ልንነው የምንችለው ሰው አልመጣልንም፤ ሌላው ቀርቶ የሙዚቃ ባንድ እና ዘፈን ዘርፍ ውስጥ መጣን፣ የበፊቶቹን ኦርኬስትራ ቡድኖች የሚተካ፣ ወይም ሁሌም ልብ የሚያሸብሩትን ዘፈኖች እና ዘፋኞች ይተካል ብለን የምንጠራው ዘፋኝ አልነበረንም… ምናልባት እጅጋየሁ ሽባባው… ተባባልን፡፡ ከጋዜጠኞችም ለማወዳደር ሞካክረን ነበር፣ እነ ጳውሎስ ኞኞን፣ እነ ታደሰ ሙሉነህን የሚተካ ቀርቶ ተስፋ የሚጣልበት ጋዜጠኛ አለ?

በየጊዜው በናፍቆት የምንጠብቀው የጋዜጣ ወይም የመጽሔት አምድ/አምደኛ፣ የሬዲዮ ወይም የቴሌቪዥን ትዕይንት፣ ልባችን እስኪጠፋ በጋራ የምናደንቀው ወጣት ባለሙያ ወይም ጀግና… ብቻ በጥቅሉ ምንም የለንም፡፡

ችግሩ የኛ አለማወቅ ነው፣ ወይስ አማተሮቹን ከአንጋፋዎቹ ጋር ማወዳደራችን የሚል ጥያቄም ተከስቶብኝ ነበር፤ ይሁን እንጂ እነዚህን የምናደንቃቸውን አንጋፋ ባለሙያዎች የምናደንቅላቸው የወጣትነት ሥራዎቻቸውን እንጂ አሁን በስተርጅና የሠሯቸውን (ያውም ካሉ) አለመሆኑን ሳስብ ችግሩ የእውነት የወቅቱ የፈጠጠ ችግር መሆኑ ታሰበኝ እና እንድንነጋገርበት ይዤው መጣሁ፡፡

ኢትዮጵያ እንዴት ሰለጠነች?

ለውይይታችን ማጠናከሪያ፣ ኢትዮጵያን የማዘመን ሙከራዎች በየመንግሥታቱ መሞካከራቸውን እያስታወስን ከነዚህ ውስጥ ዐብይ ለውጥ ያስከተሉትን ጥንታውያን የዘመናዊነት እንቅስቃሴዎች እና የሀያኛውን ክፈለዘመን እርምጃዎች እያየን ዘንድሮ ላይ እንደርሳለን፡፡

Tuesday, October 23, 2012

ዳያስፖራው ጽንፈኛ ወይስ ተስፈኛ?

ከነበረበት ባሕል፣ ተመሳሳይ ቋንቋ ተናጋሪ ማኅበረሰብ፣ የኑሮ ዘዬ ወይም ባጭሩ ከነበረበት አገር (በማንኛውም መልኩ) ለቆ ወደ ሌላ አገር ለተወሰነም ሆነ ላልተወሰነ ጊዜ እየኖረ ያለ ሰው/ማኅበረሰብ ቀድሞ ለነበረበት አገር ሰዎች ‹ዳያስፖራ› ይባላል (dispersed; disaspora /የፈለሰ፤ ፈላሻ እንደማለት)፡፡ አገርኛ ስናደርገው ደግሞ ከኢትዮጵያ ወጥቶ ከኢትዮጵያ ውጪ ባሉ የዓለም ክፍል ተበትነው የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንን ዳያስፖራ እንላቸዋለን፡፡ ‹‹የዳያስፖራ ፖለቲካ›› ስንል ደግሞ ዳያስፖራ በሆነው ማኅበረሰባችን የሚንፀባረቀውን ፖለቲካዊ አቋም፣ አመለካከት እና እንቅስቃሴን ማለታችን ነው፡፡ በተለይ አሁን አሁን ስለአገራችን ማኅበራዊና ፖለቲካዊ ጉዳዮች ‹ዳያስፖራው ምን አለ?› የሚለው ጥያቄ የማይሻር ጉዳይ እየሆነ ነው፡፡ ሆኖም ደግሞ በጉዳዮች ላይ የተሰጡ አስተያየቶችን አይቶ ከኢትዮጵያ ውጪ በሚኖር ሰው የተሰጠ መሆኑን እና አለመሆኑን ለማወቅ ቀላል እየሆነ እንደመጣ የሚከራከሩም አሉ፡፡ እነዚህም፡-


  •  በተለምዶም የአስተያየቱን ጽንፉን ተመልክቶ ‹የዲያስፖራ ፖለቲካ›› የሚባል ስያሜ እየተሰጠው ይገኛል፡፡ የ‹የዳያስፖራ ፖለቲካ› ውስጥ በብዛት ጽንፉ ወዲህ ወይም ወዲያ ይሆን ይሆናል እንጂ ፅንፍ መያዙ አይቀርም የሚለው እምነት የብዙዎች እየሆነ ነው፤ እንዲያውም አንዳንዶቹ ሁለቱንም ጽንፎች አዳርሰዋል በሚል ሰለሞን ተካልኝ በማስረጃነት ያነሳሉ፡፡
  •  ዳያስፖራው እኛ (በአገር ውስጥ ነዋሪዎች) የማናውቀውን የዴሞክራሲ ጣዕም የሚያውቅ፣ እኛ የሌለን የፖለቲካ ምኅዳር ያለው፣ ገሚሱ ኑሮው ሞልቶለት የወገኑ ጉዳይ ከሩቅ የሚቆረቁረው የለውጥ ተስፈኛ እንጂ ጽንፈኛ ሊባል አይገባውም የሚሉት ደግሞ በሌላ ወገን ይገኛሉ፡፡

በርግጥም ጽንፍ የያዙ እና ማንኛውንም ዓይነት በአገራችን ውስጥ የሚታዩ እንቅስቃዎችን ጥቃቅን ጉድለቶችን እየነቀሱ በማውጣት፣ በማጉላት እና ጠንካራ ትችት ማቅረብ የዳያስፖራ ፖለቲከኞች መለያ እየሆነ ነው እንዲያውም ዋነኛ ዓላማቸው መቃወም እንጂ ለለውጥ መትጋት አይደለም ቢባልም፣ የእውነተኛ ለውጥ መንገድን ለማምጣት ገንዘባቸውን፣ ዕውቀታቸውን እና ጊዜያቸውን እየፈሰሱ ያሉትም ‹‹ከኑግ የተገኘሽ መጭ አብረሽ ተወቀጭ›› በሚል ሰበብ አብረው እየተጨፈለቁ ነው፡፡ ጉዳዩን በኮንትሮባንድ ውስጥ ለውስጥ ከማስኬድ ይልቅ በመወያየት የሚበጀውን አካሔድ በጽንፍ/ተስፋ ቅጥያ ሳንከፋፈል እንድንሄድበት ማድረግ የዚህ ጽሑፍ ዓላማ ነው፡፡  

ምንም እንኳን እነርሱ ከሌሉበት (አስተያየታቸውን ካልሰጡበት) የኢትዮጵያ ፖለቲካ ነፍስ የሌለው በድን ይሆናል የምንላቸው ዳያስፖራዎች ቢኖሩም፣ ይህ ጽሑፍ ግን ባመዛኙ ‹‹ስንዴውን ከገለባ ለመለየት›› ሲባል ሊወቀሱ የሚገባቸውን መውቀስ ላይ ያተኩራል፡፡ ሊወቀሱ የሚገባቸው የምንላቸው እነዚህን ያካትታል፡-
·         ኢትዮጵያ ውስጥ የተከሰተውን የፖለቲካ ምኅዳር መጥበብ የግል መጠቀሚያ (መተዳደሪያ) ከማድረግ ውጪ ፖለቲካ ያለ ለማይመስላቸው፣
·         በተለያዩ አደጋዎች የደረሰባቸውን አደጋ መንግስት እንዳደረሰባቸው በማስመሰል የሐሰት ትዝብት በመፍጠር ላይ ላሉ፣
·         ለምክንያት (causes) ሳይሆን ለጥገኝነት መጠየቂያ ሲባል ብቻ የመሪዎችን መምጣት ተከትሎ የሚደረጉ ሰልፎች መብዛት፣
·         ይህንና ይህን መሰሎች ችግሮች እያሉባቸው ጉዳዩን እንዳይወራ ለማነወር እየጣሩ ያሉ ቀጥተኛ ተጠያቂ ዳያስፖራዎችን ነውሩን ለመጠየቅ ነው፡፡

የአንድ “ተራ” ዳያስፖራ አመለካከት እዚህ አገር ካለ ፖለቲከኛ ይልቅ (ዕድሜ ለቴክኖሎጂ እና ሐሳብን ለመግለጽ ነጻነት) ሕዝቡ ጓዳ የመግባት ዕድል ያለው እየሆነ ነው፤ ስለሆነም የጎበጠ የሚመስለንን ለማቅናት እና የተቃናውን ደግሞ ለመጠናከር መወያያ ጊዜው አሁን ነው፡፡ ለውይይት እንዲያመቸንም አንድ በሚያደርጓቸው ባሕርያት እየከፋፈልን እንመለከታቸዋለን፡-

ጫና ያሳደዳቸው

የአገራችን ፖለቲካና ማኅበራዊ ጉዳዮች ላይ በማተኮር የሚጽፉ እና የተበደሉ ሕዝቦችን ድምፅ ባገኙት አጋጣሚ ሲያሰሙ የነበሩ ጋዜጠኞች፣ ጸሐፊዎች እና የሰብዐዊ መብት ተሟጋቾች እዚህ ምድብ ውስጥ ይገኛሉ፡፡ አገር ውስጥ እያሉ በሠሯቸው ሥራዎች ዕውቅናን ያተረፉና የሕዝብን ጆሮ አግኝተው የነበሩ ብዙ ናቸው፡፡ እነዚህ ሰዎች የሕዝቦቻቸው ልሳን በመሆናቸው ብቻ በስልክ ከሚደርሳቸው ማስፈራሪያ እና ዛቻ አንስቶ ለአካላዊ ጉዳት የመዳረግ፣ የመንገላታት እና የመታሰር ዕጣ ሊደርስባቸው እንደሚችሉ ጥቁምታዎች ወይም ምልክቶች በሚያገኙበት ጊዜ በተለያየ ምክንያት አገራቸውን ለቀው ለመሰደድ ይወስናሉ፡፡

እነዚህኞቹን በተመለከተ አገር ውስጥም ባሉ ሆነ ቀድሞውንም በተሰደዱ ሰዎች ‹‹መሰደዳቸው አግባብ አይደለም፤ እዚሁ ሆነው እስከ መጨረሻው ድረስ የሚደርስባቸውን ሁሉ ማለትም እስሩንም፣ እንግልቱንም፣ፍትሕ ማጣቱንም ከሕዝባቸው ጋር እንደጀመሩት መጨረስ ነበረባቸው›› የሚል አመለካከት ያላቸው ሰዎች ያሉትን ያክል ‹‹የለም፤ እነዚህ ሰዎች እስር ቤት ገብተው ለራሳቸውም ከሚንገላቱ፣ ወጥተው የቻሉትን ያህል ሕዝባቸውን በአቋራጭ ቢታገሉለት፤ በዚያውም ለዓለም አገር ውስጥ ያለውን ችግር ቢያስረዱ ይሻላል›› የሚሉትም ብዙ ናቸው፡፡

ይሁን እንጂ ከሩቅ ሆነው በላፕቶፕ የሚታገሉት ሰዎች የመጀመሪያውን ሲናገሩ አገር ውስጥ ካሉት ይልቅ የበለጠ ያስከፋል፡፡ ለዚያም ነው ‹‹እነርሱ ሊኖሩት ያልፈቀዱትን ሌሎች እንዲኖሩ ግፊት ያደርጋሉ›› በሚል በጽንፈኝነት የሚከሰሱት፡፡

በተረፈ ግን ብዙዎቹ በዚህ መንገድ ተሰደው የወጡ ጋዜጠኞችን እንደምሳሌ ብንወስዳቸው ባመዛኙ ከጽንፈኝነ የፀዱ ሆነው እናገኛቸዋለን፡፡ የአዲስ ነገር ጋዜጠኞች፣ የአውራምባ ታይምሱ ዳዊት ከበደ፣ የፍትሑ አበበ ቶላ፣ እና እንደ አርጋው አሽኔ ያሉ ነጠላ ስደተኞች፣ ከተሰደዱ ወዲህ በተለያዩ አምባዎች እና ማኅበራዊ አውታሮች ከሚያሰፍሯቸው ጽሑፎች ውስጥ መረዳት እንደምንችለው፣ አንደኛ በስደት ሆነውም ብዙዎቹ አገር ውስጥ ሆነው የነበራቸውን አቋም ቀጥለውበታል፤ ሁለተኛ ከተሰደዱ ወዲህ ያሉ ወቅታዊ ጉዳዮችን በመከታተል ራሳቸውን ከአገር ውስጥ መረጃዎች አላራቁም፣ ሦስተኛ የአገር ውስጥ እውነታዎችን በተዛባ ሁኔታ አይረዱም፣ ወይም ለግል ጥቅማቸው መጠቀሚያነት ሲረባረቡበት አልታዩም፣ አራተኛ እነዚሁ ሰዎች የስርዓት ለውጥ ከመጣ ተመልሰው መጥተው እኛኑ ነውና ‹‹ጽንፈኛ›› በሚለው አብረን ልንፈርጃቸው አይገባም፡፡

የዳያስፖራ ተቃዋሚ ፓርቲ/ቡድን አመራሮችና እና አባላት

በርካታ የቀድሞ ተቃዋሚ ፓርቲ አመራር አባላት ተሰድደዋል፡፡ በተለይም የፈረሰው የቅንጅት አባላት ከነበሩት ውስጥ ጥቂት የማይባሉት በስደት የየራሳቸውን ቡድን እና ፓርቲ መስርተዋል፤ ከነዚህ ውስጥ እንደምሳሌ የዶ/ር ብርሃኑ ነጋ ግንቦት ሰባት አንዱ ነው፡፡ በሌላ በኩል የኦባንግ ሜቶ ለአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄ፣ የዶ/ር ፍስሐ እሸቴ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ሽግግር ምክር ቤትም ሳይጠቀሱ የማይታለፉ ናቸው፡፡ እዚያው ለረዥም ዓመታት ነዋሪ የነበሩ፣ በተለይም በደርግ ዘመን የተሰደዱ በርካታ የኢሕአፓ ሰዎችም ፖለቲካው ውስጥ በግልም በቡድንም አይጠፉም፡፡

እነዚህንም በተመለከተ ሁለት አመለካከቶች አሉ፤ ምንም አልሠሩም/አይሠሩም እና ያቅማቸውን እየሠሩ ነው የሚሉ፡፡ ነገሮችን በምሳሌ መመልከቱ እየሠሩ ያሉትን እና ያላግባብ ስም እየፈሱ ያሉትን ለመለየት እና ወደፊትም እየጠየቅን ምስጋናችንን/ድጋፋችንን እንድንችር ያደርገናል፡፡ እነሆ ምሳሌዎቹ፡-


  • በገዢው ፓርቲ በአሸባሪነት የተፈረጀው እና ግዝፈቱ እና አስፈሪነቱ በቴሌቪዥን የሚደሰኮርለት ግንቦት ሰባት እስከአሁን ድረስ የሠራው ሥራም ሆነ ያሸበረው ሽብር ምን እንደሆነ ቢጠየቅ፣ ተቃውሟቸውን በይፋ ለሚገልፁ ሰዎች ‹‹ባጅ›› በመሆን ለመንግስት ከማገልገል ውጪ ይሄ ነው የሚል መልስ  ለማግኘት አስቸጋሪ ይሆናል፡፡ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ሽግግር ምክር ቤት መነሻዬ ያለውን ለኢትዮጵያ የስርዓት ለውጥ የተዘጋጀ የሽግግር መንግስት የማዋቀር ሥራውን ትቶ በቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር የሞት ቀን ላይ (እንደ መረጃ ሰጪ ሚዲያ) የጦፈ ክርክር በማድረግ የትኩረት አቅጣጫውን ስቶ ታይቷል፡፡ ሲመሠረት በሁለት ወራት ውስጥ፣ የአቶ መለስ ኅልፈት ከተሰማ ወዲህ ደግሞ በሁለት ሳምንት ውስጥ የኢትዮጵያን ሕዝብ ነጻ አወጣለሁ ብሎ ቃል የገባው ይሄው የሽግግር መንግስት ቃሉ ከተግባሩ የፈጠነ መሆኑ ሌሎች የዳያስፖራ ቡድኖችንም ሆነ እራሱን ከተኣማኒነት ዝርዝር ውስጥ በዚህ መንገድ እንዳያወጣ ያሰጋል፡፡
  • EAC (Ethiopian Americans Council) በመባል የሚታወቀው ቡድን በተቃራኒው፣ በተቃራኒው ለኦባማ ደብዳቤ ከመጻፍ አንስቶ፣ በልማት ሰበብ የሚገኙ የእርዳታ ገንዘቦች ነጻነትን ማፈኛ እንዳይወሉ የማንቂያ ደውል ለአሜሪካ መንግስት በመደወል እየሰሩ ያሉት የሚበረታታ ነው፡፡ የጋራ ንቅናቄ የተባለውም ቡድን በተለይ በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ የአቋም መግለጫ ጽሑፎችን በማውጣት ይታወቃል፤ አሁንም እንኳን በቅርቡ ለጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ለውጥን የሚጠይቅ ግልጽ ደብዳቤ አሰራጭቷል፡፡ የHR2003 (የሰብኣዊ መብት ጉዳይን ያስቀደመ መመሪያ) የአሜሪካ መንግስት የኢትዮጵያ መንግስት ላይ እንዲጥል አሊያም እርዳታ እንዲያግድ የሚያደርገውን ዶሴ በማርቀቅ እና እንዲፀድቅ እና አገር ውስጥ ለውጥ እንዲመጣ ጫፍ ደርሶ የነበረ ትግል የታገሉትም የዳያስፖራ ቡድኖች ናቸው፡፡ ይህንን በምክንያት ከመሟገት እና ለውጥን ከመወትወት ወይም የ‹‹አራማጅነት›› ሚና የተሻለ የሚሠሩ እና ሊበረታቱ የሚገባቸው አሉ፡፡


በተለያየ የፓለቲካ ግብ ውስጥ የሚንቃቀሱ የፓለቲካ ቡድኖች ምንም እንኳን የፓለቲካ አቋማቸውን በሚደግፍ መልኩ መረጃዎችን መተንተናቸው የሚያስቀወቅሳቸው ባይሆንም፣ ቡድኖቹ ግልጽ ባልሆነ የፖለቲካ ዓላማ እና የሕዝቡን ነባራዊ ፍላጎት እና ሁኔታ ከግምት ውስጥ ባላስገባ እንቅስቃሴ የሚሰጡት ትንታኔ አቅጣጫ ወይም መረጃ አምታች እና አወናባጅ መሆን የለበትም፡፡ ይህ ዓይነቱ ችግር አገር ውስጥ ያሉትም የፖለቲካ ቡድኖች ቢሆንም በዳያስፖራዎቹ ይጋነናል የሚል እምነት አለን፡፡ ውሸት ይነግሩናል ባንልም ከነርሱ ጋር የሚያሟግተንን እውነት ሊደብቁን፣ ወይም ለነሱ ፍላጎት የሚያመዝነውን ብቻ ሊያስተጋቡልን ይችላሉ የሚለው ስጋት አገር ውስጥ ባለው ወገን ዘንድ የሚፈጠረውም ይሄን ጊዜ ነው፡፡

ለመኖሪያ ፈቃድ ሲባል…?

ለትምህርት፣ ለስልጠና፣ ለወርክሾፕ፣ ለስብሰባ፣ ለጉብኝት እና በመሳሰሉ ምክንያቶች ከአገር ወጥተው በዚያው ቀልጠው የሚቀሩ ሰዎች ቁጥር ቀላል አይደለም፡፡ እነዚህ ሰዎች አሁን አሁን እንደፋሽን የሚጠቀሙበት የፖለቲካ ጥገኝነት መጠየቅን ነው፡፡ የፖለቲካ ጥገኝነት ጠያቂዎቹን በሁለት ከፍለን ልናያቸው እንችላለን፡፡ የመጀመሪያዎቹ፤ በሚሄዱበት አገር የፖለቲካ ጥገኝነት ሊያሰጣቸው የሚያስችል ቅድመ ዝግጅት አገር ውስጥ በነበሩበት ወቅት የሚያደርጉ ናቸው፡፡ የተቃዋሚ ፓርቲ መታወቂያ ለማግኘት መጣር፣ መንግስትን በመተቸት ከሚታወቁ ሰዎች ጋር ፎቶ መነሳት እና መንግስትን የሚቃወሙ ጽሑፎችን በግል የሕትመት ሚዲያዎች በስማቸው ማውጣትን በምሳሌ ማንሳት እንችላለን፡፡ አጋጣሚውን አግኝተው ከዚህ አገር በሚወጡበት ወቅት ቀድመው ያዘጋጇቸውን ምክንያቶች እንደማስረጃ በማቅረብ የፖለቲካ ጥገኝነት ጥያቄ ያቀርባሉ፡፡ በሁለተኛው ክፍል የምናገኛቸው ደግሞ ከላይ በጠቀስናቸው ባንዱ ምክንያት ከአገር የመውጣቱን አጋጣሚ ድንገት ያገኙና  ምንም ዓይነት ቅድመ ዝግጅት ሳያደርጉ የሚወጡ ናቸው፡፡ ካገር ሲወጡ እዛው የመቅረትን ጉዳይ በአዕምሮአቸው የነበራቸው ቢኖሩም የመመለስ ዕቅድ የነበራቸው እና እዛው ባሉበት ሐሳባቸውን ቀይረው ለመቅረት የወሰኑም ይገኙበታል፡፡ 

ሁለቱንም ቡድኖች የሚያመሳስላቸው በሄዱበት ለመቅረት ያላቸው ፍላጎት፣ መኖሪያ ፈቃድ ለማግኘት የፖለቲካ ጥገኝነት መጠየቃቸውና የሐሰት መረጃዎችን ለሚመለከተው ክፍል ማቅረባቸው ነው፡፡ በመጀመሪያው ቡድን ያሉት ቀደም ብለው በጉዳዩ ላይ ተዘጋጅተውበት በመውጣታቸው እንደሄዱ ማመልከቻቸውን በማስገባት  ባጭር ጊዜ ውስጥም ሊሳካላቸው የሚችል ሲሆን በሁለተኛው ቡድን ያሉት ግን የሐሰት መረጃዎችን ማሰባሰብ የሚጀምሩትና የሚያገኙት ከጥቂት ቆይታ በኋላ አንዳንድ ጊዜም የቪዛቸው ጊዜ ወደማለቁ አካባቢ ወይም ካለቀ በኋላ ስለሚሆን ለብዙ መጨናነቅ፣ ወጪና እንግልት ይዳረጋሉ፡፡ እንዲህም ሆኖ መኖሪያ ፈቃድ የማግኘታቸውና ያለማግኘታቸው ጉዳይ እኩል፣ እኩል ነው፡፡

እንደነዚህ ዓይነት “ዳያስፖራዎች” (በትዕምርተ ጥቅስ) ብዙዎቹ ስለአገራቸው የፖለቲካ ታሪክ እና ወቅታዊ ፖለቲካና ማኅበራዊ ጉዳዮች ጠለቅ ያለ መረጃ ባይኖራቸውም፣ መንግስትን የሚቃወም የማንኛውንም ግለሰብም ሆነ ድርጅት ሐሳብ ያስተጋባሉ፡፡ ለዚህም በዋነኝነት ፌስቡክ እና ትዊተርን ጨምሮ የተለያዩ ማኅበራዊ አውታሮች፣ ጦማሮችን እና ድረገጾችን እንደመሳሪያነት ይጠቀሙበታል፡፡ ባለስልጣናት ለሥራም ሆነ ለስብሰባ እነሱ ወዳሉበት ቦታ በሚመጡበት ጊዜም - ነባር፣ በእውነተኛ ተቃውሞ ጦስ ተሰድደው የወጡ የዳያስፖራ አራማጆች በሚያስባብሯቸው - ተቃውሞዎች ላይ መታደም እና በቦታው መገኘታቸውን የሚያሳይ መረጃ መያዝ ተቀዳሚ ሥራቸው ነው፡፡

በተጨማሪም በአገራችን የሚካሄዱ ኢ-ፍትሐዊ ድርጊቶችን በመቃወም የሚደረጉ ሰልፎችና አላግባብ የታሰሩ ዜጎችን ለማስታወስ የሚዘጋጁ ፕሮግራሞች ላይም ቁጥር አንድ ተሳታፊ ናቸው፡፡ ምናልባትም ከፕሮግራሙ ርዕስ በዘለለ የተዘጋጀበትን ምክንያት እና ዓላማ ላያውቁ ይችላሉ፡፡ ባጭሩ በዚህ ምድብ የሚገኙ “ዳያስፖራዎች” አብዛኛዎቹ ማለት ይቻላል የኔ የሚሉት ፖለቲካዊ አቋምም ሆነ አመለካከት የሌላቸው ሲሆን ዋነኛ ሥራቸው በመንግስት ላይ የሚሰነዘርን ማንኛውም ዓይነት ተቃውሞ ባገኙት አጋጣሚ ሲያስተጋቡ መታየት ወይም መሰማት ነው፡፡ እነዚህ ጠቅላላውን የ‹ዳያስፖራ ፖለቲካ› ውጤታማነት እንዴት እንደሚያውኩት በሚከተሉት ምሳሌዎች መረዳት ይቻላል፡-


  • የተቃውሞ ሰልፎች እና ስብሰባዎች ላይ የሚሳተፉ እነዚህ ለፖለቲካው ጤንኝነት ደንታ የማይሰጣቸው ሰዎች ‹‹ጥገኝነት›› ፈላጊዎች ግንባር ቀደም እና አርማ ተሸካሚ ሆነው በፎቶ እና ቪዲዮ ማኅበራዊ አውታሮች ላይ በአጋጣሚ የሚመለከቱ እና ግለሰቦቹን የሚያውቋቸው የአገር ቤት ሰዎች ጠቅላላ የዳያስፖራውን እንቅስቃሴ በግለሰቦቹ ዓይን የመዳኘት እና በኢቴቪ ፕሮፓጋንዳ ‹‹ጥገኝነት ለመጠየቅ ሲሉ›› የሚለውን የሚያረጋግጥ ማስረጃ ስለሚሆን፣
  • ግለሰቦቹ የጥገኝነት ወረቀታቸውን ካገኙ በኋላ ተመልሰው ትግሉን ስለማይቀጥሉበት፣ መጣ ቅርት የሚሉ አራማጆችን መመልከቱ/መከታተሉ ተስፋ ስለሚያስቆርጥ፣
  • ግለሰቦቹ ወረቀቱን እስከሚያገኙ ድረስ ፖለቲካዊ ተሳትፏቸውን ለማጉላት እና ተቃዋሚነታቸውን ለማሳመን ጽንፍ ድረስ ስለሚጓዙ የጠቅላላውን ዳያስፖራ መልክ በአንድ ላይ የማጉደፍ ኃይል አላቸው፡፡

እነዚህን ግለሰቦች በጥንቃቄ መጠቀም ያልቻለ የዳያስፖራ ማኅበረሰብ ወይም ዝግጅት አስተባባሪ፣ ወይም በጥንቃቄ መከታተል ያልቻለ የአገር ውስጥ ነዋሪ መስመሩን የሳተ ግንዛቤ ስለዳያስፖራዎቻችንም ሆነ ስለአጠቃላይ እንቅስቃሴያቸው ያኖራል፡፡

የዳያስፖራ ሚዲያዎች

በተለይም በፖለቲካው ዙሪያ መረጃ እና ትንታኔዎችን የሚያቀርቡ በርካታ፣ ባብዛኛው ኢንተርኔት ላይ ጥገኛ የሆኑ መገናኛ ብዙሐን አሉ፡፡ ከነዚህ ውስጥ በድረገጽ የሚሰሩት እነኢትዮሚዲያ፣ ዘሐበሻ፣ ኢትዮጵያንሪቪው፣… እና አሁን እየጎሉ ከመጡት ውስጥ ደግሞ ጎልጉል ሳይጠቀሱ አይታለፉም፡፡ እነዚህ መገናኛ ብዙሐን በተለይ ገዢው ፓርቲን በሚቃወሙ መጣጥፎች ላይ ምንም መመዘኛ የሌላቸው እስኪመስል ድረስ፣በአገራዊ ስነምግባራዊ እሴቶች የሚያስገምቱ ስድቦችን በማስተናገድ ጭምር ይታወቃሉ፡፡ ከነርሱ በተቃራኒው የቆሙት እና የገዢው ፓርቲን በማንቆለጳጰስ ሥራ ተጠምደው፣ ዓላማቸው ‹‹አማራጭ ሚዲያ›› መሆን ይሁን ወይም ካድሬነት የማይለዩት እነአይጋፎረም፣ ኢትዮጵያፈርስት እና ትግራይኦንላይን የመሳሰሉት ድረገጾች ደግሞ ተቃዋሚውን እስካዋረደላቸው ድረስ የሚያሰራጩት መረጃ እውነት ይሁን ሐሰት እንኳን ለማጣራት አይጨነቁም፡፡

በዚህ መሐል የሚዲያዎቹን ማንነት እና እሴት የማያውቀው አንባቢ በከፍተኛ ደረጃ ይጎዳል፡፡ አሁን በተቃዋሚ ወገን የምንመድባቸው በሙሉ በኢትዮጵያ እንዳይነበቡ በመታገዳቸው በፊት በኢትዮጵያ ከፍተኛ ጎብኚ የነበራቸው እነናዝሬት እና ኢትዮጵያንሪቪው ከዝርዝሩ ወጥተው፣ ከፍተኛ ተነባቢነት ያላቸው እነትግራይኦንላይን መሆናቸውን የአሌክሳ ዌብ ትራፊኪንግ መረጃ ያመለክታል፡፡ ይሁን እንጂ የታገዱትን ገጾች ዜናዎች በዚህም ሆነ በዚያ እያሉ (በተለይ በማኅበራዊ አውታሮች) በኩል የሚያገኙት ብዙሐን ናቸው፡፡

ከዚህ በፊት የአገር ውስጥ ጋዜጦች መለስ በመልካም ጤንነት ላይ ናቸው ብለው በማለታቸው ይቅርታ እንዲጠይቁን ወትውተን እንደነበር ይታወሳል፡፡ ከዳያስፖራ መገናኛ ብዙሐን መካከልም፣ በተለይ ኢትዮጵያንሪቪው ብዙ ባለስልጣናትን እና ባለሀብቶች ሳይቀር ሞተዋል፣ ተሰደዋል የሚሉ ዜናዎችን ጽፎ አንብበን ከጥቂት ጊዜ በኋላ ስህተት መሆኑን ሰምተናል፡፡ በተመሳሳይ እነርሱም ይቅርታቸው ይገባን ነበር፡፡ ምንም እንኳን ይህ ጽሑፍ ይህንን ርእስ ለማንሳት ባያስብም የተአማኒታቸውን ነገር ግን ችላ ማለት አይገባም፡፡፡ 
የኢትዮጵያ ሳተላይት ቴሌቪዥንም እዚህ ምድብ ውስጥ ይካተታል፡፡ የኢትዮጵያ ሳተላይት ቴሌቪዥን የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን የዳያስፖራ እኩያው ነው መባል ከጀመረ ሰንብቷል፡፡ በፅንፈኛነት ስሙ መነሳት ከጀመረ ሰነባብቷል፡፡ ለዚህ እንደምክንያት የሚጠቀሱት፣ ሙያዊ ስነምግባር (professional ethics) ላይ እምብዛም አለመጠንቀቃቸው፣ ከዜና እና ዜና ነክ ትንታኔዎች በላይ አንጀት አርስ ፕሮግራሞችን አለመሥራታቸው፣ ከአገር ቤት ጋር የሚገናኙ ጥቃቅን የሁከት ዜናዎችን ማጋነናቸው ሳይጠቀሱ የማይታለፉ ድክመቶች ናቸው፡፡ አማራጭ መገናኛ ብዙሐን በሌለበት ኢሳትን አለማመን ቢከብድም፣ ኢሳት ይህንን ግዳጁን በሙሉ ኃላፊነት እንዲወጣ እና በሙሉ ልብ እንዲታመን ገና ብዙ ይጠበቅበታል፡፡

እርግጥ ነው፣ እነዚህ መገናኛ ብዙሐን እዚህ አገር የታፈኑ (የተነወሩ) በርካታ እውነታዎችን ለሕዝቡ በቻሉት መንገድ ሁሉ ለማድረስ በስደት ሕይወታቸው መፍጨርጨራቸው ትልቅ ዋጋ የሚሰጠው ቢሆንም ጥረታቸው ዋጋ እንዲኖረው ተአማኒነት ያላቸውን መረጃዎች ለማቅረብ መድከም አለባቸው፡፡ አለበለዚያ ስናነባቸው በጥርጣሬ እንዲሆን ልንገደድ እንችላለን፡፡

የዳያስፖራ ምሁራን እና አራማጆች

በኢትዮጵያ ያሉ ምሁራን ሙሉ ለሙሉ ሊባል በሚያስደፍር ሁኔታ ዝምታን በመረጡበት በዚህ ወቅት የኢትዮጵያ ወቅታዊ ፖለቲካ ምሁራዊ እይታ እንዳያጣ ትንሽ የረዱት የዳያስፖራ ምሁራን እና ሌሎችም ለነፃነት ተቆርቋሪ ስደተኛ አራማጆች ናቸው፡፡ እነአለማየሁ ኃይለማርያም፣ እነመሳይ ከበደ፣ ጃዋር መሐመድ እና ሌሎችም ሳይጠቀሱ አይታለፉም፡፡

የዳያስፖራ ምሁራን በተለያዩ ከላይ በጠቀስናቸው እና ሌሎችም መገናኛ ብዙሐን የሚያቀርቧቸው ትንታኔዎች ምንም እንኳን በአብዛኛው ወደሚደግፉት ቡድን ርዕዮት ያመዝናሉ የሚል ሐሜት ቢያጋጥማቸውም በዳያስፖራው ማኅበረሰብ ተአማኒነት ያለው መረጃ በመስጠት የተሻሉ ናቸው፡፡ ይህ የሆነበት ምክንያት፣ ብዙ ጊዜ መከራከሪያ ነጥቦቻቸው እውነታዎች እና ሳይንሳዊ ርዕዮተ ዓለሞች መሆናቸው ነው፡፡ በተጨማሪም እነዚህ ምሁራን የሚያቀርቧቸው ጽሑፎች እንደሌሎቹ አጫጭር መጣጥፎች ከስድብ ይልቅ አመክንዮ ይበዛባቸዋል፡፡ ስለዚህ የምሁራኑን ትንታኔ እያነበቡ የራስን ውሳኔ መውሰዱ ጠቃሚ እንደሚሆን መደምደም ይቻላል፡፡

በጥቅሉ፣ ፖለቲካ ቀመስ የሆኑ ጽሑፎችን የምናነበው ወይም የምንጽፈው መረጃ ለመለዋወጥ ያክል ብቻ ሳይሆን ለብሔራዊ ለውጥ ጉጉት ስላለን ነው፡፡ ቢሆንም ግን በአገር ውስጥም ሆነ በዳያስፖራው ውስጥ ብሔራዊ ብቻ ሳይሆን ግለሰባዊ አጀንዳ ያላቸውም ሰዎች አሉ፡፡ ይህ በተለይ በኢትዮጵያውያን ዳያስፖራዎች ላይ ያተኮረው ጽሑፋችን ዓላማም፣ የዳያስፖራ ፖለቲካ ውስጥ ‹‹ማን፣ ምን እና ለምን›› የሚለውን በማገናዘብ ሁሉንም በጽንፈኝነት ወይም በተቃራኒው የዋሕነት ብቻ ሳይቀበል እንዲመረምር በማድረግ ማኅበራዊ ተዋስኦን ማበረታት ነው፡፡

በተለይ በጉዳዩ ላይ ከዚህ በፊት በተነሱ አስተያየቶች ዳያስፖራው ለሚታማበት ጽንፈኝነት የራሳቸውን ምክንያት የሚዘረዝሩ አሉ፡፡ ከነዚህ ምክንያቶች ውስጥ እኛ (በአገር ውስጥ ነዋሪዎች) በባሕላዊ አስተሳሰቦች እና በዴሞክራሲ መብት እጦት የታፈነ ማኅበረሰብ ውስጥ የነጻነትን ትክክለኛ ትርጉም እና ጣዕም በአግባቡ ማጣጣም ባለመቻላችን የመጣ ክፍተት እንደሆነ የሚናገሩ አሉ፡፡ በተጨማሪም፣ አንዳንዴ የነጻነትን ትክክለኛ ጣዕም ያጣጣሙ ስደተኞች ያን ዓይነቱ ለውጥ ወደአገር ቤት በተቻለ ፍጥነት እንዲመጣ ማሰባቸውም ለአንዳንድ ስህተቶች እንደሚዳርጋቸው ይታመናል፡፡ ዞሮ፣ ዞሮ እዚህም ያለነው ወይም እዚያ ያሉት የምንታገለው ለጋራ ለውጥ ስለሆነ እነርሱም እኛን፣ እኛም እነርሱን የምናደምጥበት መድረክ እና ቋንቋ ያስፈልገናል፡፡

የኢሕአዴግ ስርዓት፤ ፍጹም የበላይነት ወይስ የሕግ የበላይነት?



ይህ ጽሑፍ የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት ባካሄደው ሕዝባዊ ስብሰባ ላይ ካቀረብኩት ንግግር የተወሰደ ነው፡፡ ከሁሉ አስቀድሞ በስብሰባው ላይ ተገኝቼ ንግግር እንዳደርግ ዕድል ለሰጠኝ ፓርቲ ምስጋናዬን አቀርባለሁ፡፡

በቃል የቀረበውን በጽሑፍ ለማሰናዳት የፈለግኩበት ምክንያት በመጀመሪያ በጽሑፍ ሲቀርብ ሰፋ ላለ አንባቢ ተዳራሽ ስለሚሆንና በሁለተኛ ደረጃ ይህን መጽሔት [አዲስጉዳይ] ጨምሮ በሌሎች የሕትመት ውጤቶች ላይ ሲስተናገድ ትክክለኛው የሐሳብ ምስል ስላልቀረበ ምናልባት በዚህ ጽሑፍ የተሟላ መልዕክቱን ማስተላለፍ ይቻላል በሚል እምነት ነው፡፡…

ታሪክና ፍልስፍና
የሰው ልጅ በብዙ መልኩ ከታሪክ ሊማር ይገባዋል፡፡ ሆም ግን የረዥም ጊዜ የታሪክ ሒደት የሚያሳየው ሰው ከታሪክ መማር እንደሚያዳግተው ነው፡፡ ይህንንም ትዝብት ታላቁ የጀርመን የ19ኛው ክፍለዘመን ፈላስፋ ሄግል ‹‹ታሪክ የሚያስተምረን ነገር ቢኖር የሰው ልጅ ከታሪክ አለመማሩን ነው›› ሲል ገልጾታል፡፡

ኢሕአዴግም ሆነ የተቃዋሚ ፓርቲዎች በተለያዩ ጥያቄዎች ላይ ኢ-ታሪካዊ አቀራረብ እንዳላቸው ለማየት አያዳግትም፡፡ ኢሕአዴግን በተመለከተ የድርጅቱ ምሁራን ታሪክን የሚጠቅሱት አንድም ካለፈው የተሻሉ መሆናቸውን ለማስረዳት አሊያም በፍፁም ከዚህ በፊት ያልነበረ አዲስ ነገር የፈጠሩ አድርገው ለማቅረብ ነው፡፡

የዚህ ዓይነት የታሪክ ዕይታ ችግሩ አንደኛ ‹‹የታሪክን ቀጣይነትና ተከታታይነት›› (continuity and discontinuity) በመሠረቱ የሚድንና ላለንበት ወቅት የታሪክ አሻራ ዕውቅና የማይሰጥ ነው፡፡ በመሆኑም ኢሕአዴግ አብዛኛውን ጊዜ ትኩረት የሚሰጥ የታሪክ ቀጣይ አለመሆን ላይ ነው፡፡