Tuesday, July 15, 2014

የዞን 9 ጦማርያን አና ጋዜጠኞች የማእከላዊ ምርመራ የተፈጻመባቸው ምርመራ መጠናቀቅ



#Ethiopia #FreeZone9bloggers #FreeEdom #FreeTesfalem #FreeAsemamaw #FreeAllPoliticalPrisoners

ትላንትና ያለምንም ክስ ድፍን 80 ቀን የሞላቸው የዞን ዘጠኝ ጦማሪ ጓደኞቻቸን እና ወዳጅ ጋዜጠኞች ላይ ያካሄደውን ምርመራ መጨረሱን ፓሊስ በጓሮ በኩል ፍርድ ቤትበመቅረብ አሳውቋል፡፡ ቅዳሜ እለት 28 ቀናት የምርመራ ጊዜያቸውን ጨርሰው ወደፍርድ ቤትከመሄዳቸው ከቀናት አስቀድሞ ከነበሩበት የጨለማ ክፍል እስር በተለምዶው ሸራተን ወደሚባለው ቦታ የተዘዋወሩት ጦማርያን እና ጋዜጠኞች ላለፉት ጥቂት ቀናት በወዳጅ እና ጓደኛም ጭምር መታየት ችለዋል፡፡ 

ቅዳሜ በመቶዎች ተሰብስበው የሚጠበቁበት ችሎት ላይ ፓሊስ ብቻውን በመገኘት እና ጠበቃውን ባላካተተ ከዳኛ ጋር የተደረገ ንግግር የፓሊስ የምርመራ ፋይሉን በማጠናቀቁ ወደ አቃቤ ህግ ማስተላለፉን እና ክሱም በከፍተኛውፍርድ ቤትአንደሚታይ በማመልከት የጊዜ ቀጠሮ ፋይሉ አንዲዘጋ ጠይቋል፡፡ ታሳሪዎችም ሆነ የህግ ጠበቃቸው ባልተገኙበት ፍርድ ቤቱ የፓሊስን ጥያቄ ተከትሎ ፋይሉ የተዘጋ ሲሆን ከሰአታት ጥበቃ በኋላ በመዝገብ ቤት በኩል ጠበቃቸውና ወዳጆች ፋይሉ መዘጋቱን ለማወቅ ችለዋል፡፡ 

በተመሳሳይ ሁኔታ ትላንት ሰኞ ይቀርባሉ ተብለው ይጠበቁ የነበሩት ሌሎች ሶስት የዞን 9 ጦማርያንም ፓሊስም ሳይቀርቡ ፓሊስ በጻፈው የሶስት መስመር ደብዳቤ ምርመራ መጨረሱን አና ለአቃቤ ህግ ማስተላለፉን አሳውቋል፡፡ በመሆኑም የጓደኞቻችን ሆኑ ፓሊስ ባልተገኙበት የትላንትናው ሂደትን አስከትሎ የጓደኞቻቸን ጠበቃ አቶ አምሃ መኮንን ክሱን በሚቀጥሉት ቀናት ውስጥ ለደንበኞቻቸው አንደሚሰጥ እነደሚጠብቁና እሳቸው ባሉበት መከናወን እነዳለበት ገልጸዋል፡፡ የፓሊስን አሰራር የወንጀል ስነስርአት ህግን ያልጠበቀ ድብብቆሽ መሆኑንም አስረድተዋል፡፡

ጓደኞቻችን ቀድሞ የነበሩት የእስር ቦታ በቀን ሁለት ጊዜ 15 ደቂቃ ወደውጪ ለመናፈስ ከመውጣት ባሻገር ምንም ከውጪው አለም ጋር የመገናኘት እድል ሳይኖራቸው ከሁለት ወራት ከግማሽ በላይ ካሳለፉበት ጊዜ በመገላገል ሊጠየቁ ወደሚችሉበት ቦታ መዘዋወራቸውን ተከትሎ በጠንካራ ሞራል አና አካላዊ ደህንነት ላይ አንደሚገኙ ለመረዳት ችለናል፡፡ በቦታው ለጎበኙዋቸው ወዳጆች አንደተናገሩትም ሁሉም ራሳቸው ላይ ጥፋተኝነትን የሚመሰክር ቃል ላይ የፈረሙ ሲሆን ጦማሪ አቤል ዋበላ ለመፈረም ፍቃደኛ ባለመሆኑ እስካሁን ሌሎች ሊጎበኘት የማይችሉት ቦታ ላይ አንደቆየ ታውቋል፡፡ 

የተከሰሱት አና ምርመራ እየተካሄደባቸው ያለው በጻፏቸው ጽሁፎች አይደለም የሚል ክርክር ሲያቀርብ የነበረው ፓሊስም ጽሁፎቻቸውን ማስረጃ አድርጎ እነዳስፈረማቸው ገልጸውልናል፡፡ ለምሳሌ ያህል ጋዜጠኛ ተስፋለም ወልደየስ የሪፓርተር ጋዜጣ ሁለት ዜናዎችን በማጋራቱ ብቻ መስረጃ ተብሎበት አንዲፈርም የተገደደ ሲሆን ዜናው የመከላከያ የብሄር ተዋእጾን አና አዲሱን የይቅርታ አዋጅን የሚመለከት ሲሆን ጦማሪ በፍቃዱ ስለለውጥ የሚለው በዞን9 ላይ የተጻፉ ተከታታይ ጽሁፎቹ እነዲሁም ጦማሪ ዘላለም ክብረት ህግ መንገድ ወይስ ምርኩዝ እና ሳንሱር ድሮና ዘንድሮ የሚሉት ጽሁፎች ይገኙበታል ፡፡ 

የዞን 9 ጦማርያን በጠንካራ አካላዊና መንፈሳዊ ሁኔታ ላይ የሚገኙ ሲሆን አላአግባብ እስሩን ተከትሎ በተለያየ መልኩ አጋርነታችሁን ላሳያችሁ የዞን 9 ነዋሪያን እና የሰብአዊ መብት ጠበቆች ከፍተኛ ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡ በምርመራ ወቅት በተደጋጋሚ የተፈጸመባቸው የመብት ጥሰትም ሃሳባቸውን መግለጻቸው ትክክል መሆኑን ያረጋገጠላቸው መሆኑን አስታውሰው መጪውን የህግ ሂደት ለመከታተል እና ለታሪክ ለማስመዝገብ ዝግጁ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ 

ዞን 9 ጦማርያን ስብስብ በምንም ድብቅ ህገ ወጥ ድርጊት ውስጥ ተሳትፈን አንደማናውቅ እና ጦማሪ ጓደኞቻችን አንዲፈቱ መጠየቃችንን እንደማናቆም እያስታወስን መጪውን የህግ ሂደት በሚገባ ለመዘገብ እና የፍትህ ስርአቱን ለመፈተሽ ዝግጁ መሆናችንን በድጋሚ አንገልጻለን፡፡ 
የጦማሪ በፍቃዱና ዘላለም ጽሁፎች ሊንክ ከስር ይገኛል፡፡

--- ኢህአዴግ ሰልጣኑን በምርጫ ይለቃል?


---ለውጥን መቋቋም እና ለውጥን መፍራት


---የሥርዐት-ለውጥ-እና-ሃይማኖቶች

 

--- -የ66 ቱ አብዪቶች እና የነጻ ማህበራት ፋይዳ  

----ሳንሱር አና ህግ ትላንትና እና ዛሬ

 

--- ሕግ ምርኩዝ ነው ዱላ ? 

--- አብዩት ወይስ አዝጋሚ ለውጥ 





No comments:

Post a Comment