Wednesday, December 3, 2014

የዞን 9 ጦማርያን እና ጋዜጠኞች “የተሻሻለ ክስ” ተሰማ

Journalist Tesfalem Woldeyes
 #FreeZone9bloggers  #FreeEdom  #FreeTesfalem  #FreeAsemamaw  #Ethiopia

የዞን 9 ጦማርያን እና ጋዜጠኞች “የተሻሻለ ክስ” ተሰማ ፡፡  ጋዜጠኛ ተስፋለም ወልደየስ በልደት በአሉ የደረሱትን የንኳን አደረሰህ መልእክቶች በፈገግታ ሲቀበል አርፍዷል፡፡

በነሶልያና ሽመልስ የክስ መዝገብ 10 ተከሳሾችን የፍርድ ሂደት የሚያየው  የልደታው ከፍተኛ ፍርድ ቤት 19ኛ ወንጀል ችሎት ዛሬ ጠዋት ተሰይሞ ተሻሻለ የተባለውን የአቃቤ ህግ ክስ በቃል አዳምጧል፡፡ ክሱ አንዲሻሻል የታዘዘበትን ብይን ግልባጭ ማግኘት አልቻልንም ያሉት የተከሳሾች ጠበቆች ክሱ መቅረብ አንደማይገባው ተቃውሞ አሰምተዋል፡፡ ፍርድ ቤቱ ጠበቆች ክሱ ላይ አስተያየታቸውን አንዲሰጡ እድል አንደሚሰጥ በመጥቀስ ተሻሻለ የተባለው ክስ በንባብ ተሰምቷል፡፡

የተሻሻለው ክስ አንደቀደመው ሁሉ ዞን 9 የሚል ምንም አይነት ቃል ያልተጠቀመ ሲሆን በተለያየ ቦታ የተጠቀሰው የሽብር ቡድን ግንቦት ሰባት እንደሆነ እንድምታ ባለው ሁኔታ በተደጋጋሚ የግንቦት ሰባት ስም ተጠቅሷል፡፡ ተቀጣጣይ ቦንብ አጠቃቀምና የሽብር ተግባር ተከታታይ ስልጠናም ከግንቦት ሰባት አንደተሰጠ በደፈናው ጠቅሷል፡፡ በክሱ ውስጥ ስልጠናው በማን እና መቼ እነደተሰጠ የስልጠናው ዝርዝር ተሳትፎና ቦታ ያልተጠቀሰ ሲሆን ሊከናወን የነበረው የሽብር ተግባርም ምን አንደሆነ አሁንም አልታወቀም፡፡ ክሱ የግንቦት ሰባት ልሳን ለሆነው ኢሳት መረጃ ማቀበልንም የሰሩት የሽብር ተግባር ነው ሲል አካቶታል፡፡ 

ጦማሪ ናትናኤል ፈለቀ ተቀበለ የተባለው 48000 ብር አሁንም በድጋሚ የተጠቀሰ ሲሆን ብሩ ከማን አና ለምን ተግባር አንደተላከ በዝርዝር ያልተገለጸ ሲሆን በደፈናው ግን ለሽብር ተግባር ተብሎ በድጋሚ ተጠቅሷል፡፡ የተከሳሾችን የስራ ዝርዝር በግልጽ ለማቅረብ የሞከረው ክሱ ጦማሪት ሶልያና ሽመልስን የቡድኑ ዋና አስተባባሪ ጦማሪ በፍቀዱን ሃይሉን ጸሃፌ ጦማሪ ናትናኤል ፈለቀን የአገር ውስጥ አስተባባሪ የሚል የሽብር ስራ ድርሻ የሰጣቸው ሲሆን ሌሎቹን ተከሰሾች መስራችና አባል ናቸው ሲል አስቀምጧል፡፡ ኦነግን ከክሱ ውስጥ ከማውጣት ውጪ መሰረታዊ ለውጥ ያላሳየው የተሻሻለው ክስ ፣ የስልጠናዎቸን ዝርዝር በማን እና የት አንደተሰጡ፣ ተቀበሉ የተባሉትን የሽብር ስትራቴጂ ፣ እነዲሁም ሊሰሩት የነበረውን ሽብር ተግባር ሳያስቀምጥ አልፏል፡፡
የተከሳሽ ጠበቆች ክሱ አንዲሻሻል የታዘዘበትን ብይን ከፍርድ ቤቱ ተቀብለው ፣ አስተያየታቸውን ይዘው አንዲቀርቡ ለታህሳስ 7 ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

በዛሬው ቀጠሮ ጦማርያን እና ጋዜጠኞቹ  በጠንካራ መንፈስ እና ፈገግታ የታዩት ሲሆን ጋዜጠኛ ተስፋለም ወልደየስ ልደት ቀኑን በማስመልከት የቀረበለትን የእንኳን አደረሰህ መልእክት በልባዊ አጸፋ ሲመልስ ታይቷል፡፡ የዞን9 ጦማርያንም ለጓደኛቸን ተስፋለም ወልደየስ መልካም ልደት ለመመኘት አንወዳለን፡፡

ማስታወሻ
ዞን9 ጦማርያን አና ጋዜጠኞች ምንም አይነት ህገ ወጥ ተግባር ላይ ተሰማርተው አንደማያውቁና ክሱም ፓለቲካዊ አንደሆነ እያስታወስን ፍርድ ቤቱ የጀመረውን መንገድ በማጠናከር ለአገራቸው የሚያገባቸው ወጣት ጦማርያንን በነጻ በማሰናበት የፍትህ ስርአቱ የሚታማበትን ወገንተኛነት የመለወጥ እድሉን አንዲጠቀም ለማስታወስ አንወዳለን ፡፡

አሁንም ስለሚያገባን አንጦምራለን!
ዞን 9
Journalist Asmamaw, Blogger Atnaf and Natnael at Lideta Court Today

No comments:

Post a Comment