Friday, June 12, 2015

አሸባሪዋ ማሂ

በአለማችን ላይ እንደሰውልጅ በገዛ ፍጡሩ ላይ የሚጨክን አውሬ የለም እስከዛሬ የምንሰማቸው አሰቃቂ እና አስነዋሪ በደሎች አንዱ ሰብአዊ ፍጡር በሌላው ላይ የፈፀማቸው ናቸው፡፡ እንደዚህ ያሉ ክፉ ተግባራት በፍትህ ሽፋን በዚህ ጊዜ በአደባባይ ሲፈፀሙ ማየት ደግሞ እጅጉን ያማል፡፡
ዘመኑን የማይመጥነውና እና የሚያደርገውን ነገር በአግባቡ ማከናወን የተሳነው በመርማሪነት ማዕረግ ማዕከላዊ የሚገኙት ገራፊዎቻችን በማኅሌት ፋንታሁን እና ጓደኞቻችን ላይ ራሳቸው ማስረጃ ማቅረብ ባልቻሉበት ጉዳይ ላይ አስገድደው ‹‹አመፅ ላነሳሳ›› ነበር የሚል  ቃል አንዲሰጡ ሲገደዱ ነበር ፡፡ ማሂም በዚህ “ምርመራ” ሂደት አመፅ አነሳሳች ተብላ አልፋለች፡፡ ከዱላቸው ውጪ አመጽ ተነሳሳ ብለው  ብለው የሚያቀርቡት ፅሁፍ ባይኖራቸውም ዜጎች ተገደው ያላደረግነው አደረግን ካሉ ገራፊዎችን ለመጠየቅ ጉልበትና አቅም የሌለው ፍርድ ቤታችን የፍትህ ስርአቱን  ፍርደ ገምድልነቱን ለማስመስከር ከበቂ በላይ ነው፡፡
እያደር አዲስ የሚሆንብን ወለፈንዲው የአገራችን የኅሊና እስረኞች ጉዳይ ሁሉም ንፅኅናቸውን የሚያረጋግጥላቸው የፍትሕ ሥርዓት ባይኖርም ከተጠረጠሩበት ጊዜ ጀምሮ አሸባሪዎች ናቸው፤ ማስረጃ ባይቀርብባቸውም አንዴ ተብለዋልና ንፁህ ሆነው እያለ ንፁህነታቸውን ማስመክር ይጠበቅባቸዋል፡፡ አሁን አሁንማ አሰራሩ የማረጋገጥ ሸክሙን ከከሳሽ ላይ አንስቶ ተጠርጣሪዎቸን ንጹህነታችሁን አረጋግጡ ይላል፡፡ ብዙዎች የፍርድ ቤት ክርክርን የሚያደርጉት ፍትሕን እናገኛለን በሚል ሳይሆን የሚደረገውን ድርጊት ሕዝብ እንዲያውቀው ሥርዓቱን ሁሉም እንዲረዳው ፤ ምናልባት የተጠራጠሩዋቸው ካሉ አንዲያውቁት እድል ለመፍጠርና ይህ እንደማይገባን ለማሳየት አጋጣሚውን መጠቀማቸው ነው፤ እንጂማ በግፍ እንደሚፈረድባቸው እያወቁ  ፍርድ ቤቱንም ሆነ አሰራሩን እውቅና መስጠት አምሯቸው አይደለም፡፡ ትሁቱ ናትኤል ፈለቀ እንዳለው እያደረጉ ያሉት “Judicial activism” ነው፡፡
የምርመራ ሂደቱ ደጋግመው ቢወሩ አንደአዲስ የሚያስገርሙ ብዙ ጉዶች አሉት ፡፡ ጥፋት አለብህ ብሎ ያሰረህ መርማሪ ‹‹ጥፋቴ ምንድን ነው ትላለህ?›› ብሎ ይጠይቅሃል፡፡ ‹‹ሕገ-መንግስቱ ተከብሮ እያለ ሕገ-መንግስቱ ይከበር በማለቴ ጥፋተኛ ነኝ›› በል ብሎ ፍዳህን ያበላህ መርማሪ መልሶ ቢሮ አስጠርቶህ ስለሕግ አስጠናኝ የቤት ሥራም ሥራልኝ ይልሃል አንተን ‹‹አሸባሪውን››
ከፃፍነው፣ ስንጦምረው ከኖርነው ውጪ ሌላ አላማ ካላገኘንባችሁ ያሉ ገራፊዎቻችን ‹‹አላማችሁ ምንድነው?›› በተደጋጋሚ የሚያነሱት 24 ሰአት ሙሉ የሚደጋገም ጥያቄያቸው ነበር፡፡  ያላለቀው ግን ያለፈውን ምርመራ ዛሬ ላይ ማሂ ስትቀልድበት እንዲህ የምትል ይመስለኛል
አላማችሁ ምን ነበር?
ዓላማችን
·         የማዕከላዊ ምርመራን በመጎብኘት የምርመራ ሂደቱን ምጡቅነት እና ዘመናዊነት መታዘብ፡፡
·         ክስ ሲመሰረት እንዴት በተልከሰከሰ መልኩ እንደሆነ ለዓለም ማሳየት፡፡
·         አቃቤ ሕግ እና መርማሪ እንዲሁም ዳኛ የጆሮ ጉትቻ እና የአንገት ሃብል መሆናቸውን ማሳየት፡፡
·         የሽበር አዋጁ እንዴት abuse እንደሚደረግ በተግባር ማረጋገጥ (አንድ ሰው ከሱቅ ዳቦ ሲገዛ ቢገኝ ዳቦውን በልተህ የሽብር ተግባር ለመፈፀም ልታስብ ስለነበር ተብሎ የፀረ ሽብር አዋጁ ተጠቅሶ መከሰሰስ እንደሚችል ማሳየት እና ለዚህ ዋናው እና አስፈላጊው ነገር የመንግስት ለመክሰስ የማሰብ ፍላጎት መኖር  ብቻውን በቂ መሆኑን ማሳየት ነው)
ግባችን ደግሞ፡- የፍትሕ ሚኒስቴር እንጂ ፍትሕ እንደሌለ ማሳየት ነው፡፡
 አሸባሪዋ ማሂ
በተለያየ አጋጣሚ ሰዎች በራሳቸው ጥፋት ሲቀየሙን አልያም ሲያኮርፉን “ጥፋቱ የእኔ ይሆን?” ከሚል በተለየ አንግል ለማየት እና ለመረዳት ብዙዎቻችን ሞክረን እናውቃለን፤ በአገራችን ሃሳብን በነፃነት መግለፅ መንግስትን እንደ መዳፈር፣ መብትን መጠየቅ አሸባሪ የሚል ካባ የሚያስደርብ ኖርም ከሆነ ሰነባብቷል፤ ብዙዎች ሃሳብህን በመግለፅህ የሚደርስብንን ነገር በመስጋት ያንን ስጋት የፈጠረውን ስርዓት ከመታገል ይልቅ የአቅማቸውን የሚሞክሩትን ማስፈራራት የእለት ተዕለት ተግባራችን ሆኗል፡፡
ይህ በአንባገነን ሥርዓት ውስጥ ዜጎች ላይ የተጫነው የፍርሃት ቀንበር ራስን ከማስገዛት አልፎ ሌሎችንም ዝም ለማሰኘት እርስ በርሳችን የሸበበን የማይገባንን ሥርዓት ተሸክምን ያለአግባብ ዜጎች ላይ በደል ሲደርስ ለምን ብለን ከመጠየቅ ይልቅ ‹‹አርፈው አይቀመጡም ነበር›› የሚል በጭለማ ውስጥ ያለ የውሸት እውነት ነው፡፡
ማሂን በዞን ዘጠኝ በነበረን ጓደኝነት የራስዋ አበርክቶ ያላት ለብዙ እንስቶቻችን ምሳሌ መሆን የምትችል ብሩህ ወጣት ናት ማሂን እኔ ሳውቃት ስልክ ደውላ አዲስ መፅሃፍ ወጥቷል ናና ሸማምት፣ የመፅሃፍት ምረቃ አለ ለምን አትመጣም፤ እና ሌሎች ይህን መሰል አስተያየቶችን ነበር የምትነግረኝ ፡። የስነጽሁፍ ፍቅሯንም ከራሷ አልፎ ለእኔም ታጋራ ነበር፡፡
ስርአቱ ስርኣት አልባ ነው፣ ዜጎችን ለማሸማቀቅ በዝምታ እንዲገዙ ለማድረግ የሚታትረው ስርኣት የሚሸማቀቁ እና ዝምታን የሚመርጡ እንደሚኖሩ ሁሉ የሕግ የበላይነት የሚባል ነገር እንደሌለ የሚታያቸው ስርዓቱን ለመሞገት ዴሞክራሲያዊ መንገድ አማራጭ እንደማይሆን የሚገለጥላቸው ብዙ ዜጎችም መፈጠራቸውም ሊስቱት አይገባም፤ ሥርዓት አልበኛውን ስርዓት መካሪ የለውም በዘር እና በጥቅማጥቅም እና የፕሮፓጋንዳ ሰለባ ሆነው የተያዙትም የስርኣቱን ስርዓት አልበኝነት እና ሕገ-ወጥነትን ጀስቲፋይ ሊያደርጉት ይዳዳቸዋል፡፡
የማይቻላቸውን ለቻልሽው ማሂ ይህ የማያልፍ የሚመስለው ክፉ ቀን ቶሎ እንዲያልፍ ምኞቴ ነው፤ በሰፊው እስርቤትም እስክንገናኝ እናፍቃለሁ፡፡


መልካም ልደት እንኳንም ተወለድሽ፡፡   

No comments:

Post a Comment